Friday, September 25, 2015

መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ

  በቅmeskel dameraድሚያ ከዘመን ወደ ዘመን ያሸጋገረን ለብርሃነ መስቀሉ ያደረሰን በሀብቱ የሳበን በረድኤቱም ያቀረበን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፡፡

ከላይ በርዕሱ ያነሣነው ኃይለ ቃል ቅዱስ አትናቴዎስ የመስቀሉን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ የተናገረው ነው፡፡ አስተሀፈረ ኃጢአተ በዲበ ምድር ወሰአረ መርገመ በዲበ ዕፀ መስቀል ወአብጠለ ሞተ በውስተ ሲዖል ወነሰተ ሙስና እምውስተ መቃብር”

“በምድር ላይ ኃጢአትን አሳፈረ መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ ሞተ ነፍስን በሲዖል አጠፋ ፈርሶ በስብሶ መቅረትን በመቃብር አፈራረሰ” በማለት ጌታችን ለሰው ልጆች ነጻነት እና ድኅነት የከፈለውን የቤዛነት ሥራ በተናገረበት ክፍል የተናገረው ነው የሰው ልጆች ነጻነታቸው የተዋጀው በመስቀል ተሰቅሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በሥልጣኑ ለይቶ ዲያብሎስን በመስቀሉ ገሎ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ወርዶ ነፍሳትን ከዲያብሎስ ባርነት ከአጋንንት ቁራኝነት ከሲዖል ግዛት ነጻ አውጥቷቸዋልና፡፡


መስቀል በዓለመ መላእክት
     መስቀል በዓለመ መላእክት በጥንተ ፍጥበረት ሰባቱ ሰማያት በተፈጠሩበት ዕለተ እሑድ ሥላሴ ጽርሐ ዓርያምን ከእሳት ዋዕዩን ትቶ ብርሃኑን ነሥቶ በፈጠረበት ጊዜ በውስጧ ታቦት ዘዶርንና የብርሃን መስቀልን ቀረፀባት ይላል ሊቁ ኤጲፋንዮስ ሥነ ፍጥረትን አምልቶ አጉልቶ በጻፈበት አክሲማሮስ በተባለ መጽሐፉ ይህ በእንዲህ እንዳለ እግዚአብሔር መላእክትን ፈጥሮ በተሰወራቸው ጊዜ ዲያብሎስ እኔ ፈጠርኳቸው ባለበት ሰዓት በአለመ መላእክት በመላእክትና በዲያብሎስ በተደረገው ጦርነት መላእክት ዲያብሎስን ድል ያደረጉት በመስቀል መሣሪያነት ነው፡፡

“በሰማይ ሰልፍ ሆነ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን /ዲያብሎስን/ ተዋጉት ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ አልቻላቸውም ከዚያም ወዲያ በሰማይ ቦታ አልተገኘለትም ዓለሙን የሚያስተው ሁሉ ምድር ተጣለ መላእክቱም /ሠራዊተ ዲያብሎስ/ ከእርሱ ጋር ተጣሉ” ራዕ.12፡7፡፡

በዚህ ውጊያ መካከል የነበረውን ሁኔታ ሲገልፅ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዲያብሎስ ሁለት ጊዜ ዲያብሎስ ድል ነሳቸው በሦስተኛው ፈጣሪያቸውን ጠየቁ ፈቃድህ አይደለምን ዲያብሎስን እንድንዋጋው አሉት፤ መላእክት ፈቃዴስ ነው ግን ድል የምታደርጉበትን ኃይል እንድታውቁ ብዬ ነው ብሎ በክንፋቸው ላይ የብርሃን መስቀል ቀረጸላቸው በእጃቸው የብርሃን መስቀል አስያዛቸው ሄደው ገጠሙት “ጐየ እግዚእ ምስለ ዓርያሙ” ጌታ ሰማይን ጠቅልሎ ሸሸ ብሎ እየደነፋ ወደ ምድር ወረደ ይላል፡፡ ስለዚህ መስቀል ፀረ ዲያብሎስነቱ የታወቀው ጌታችን ከመሰቀሉ በፊት ነው፡፡ ኃይሉም የተገለጠው ያን ጊዜ ነው፡፡

በሌላ መልኩ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ የመላእክትን ምስጋና በገለጠበት እንዲህ ሲል ጽፏል “ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን ከፍ ባለ ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ አየሁት ኪሩቤልና ሱራፌል ዙሪያውን ነበሩ ለእያንዳንዱም ስድስት ስድስት ክንፍ ነበራቸው በሁለት ክንፋቸው ፊታቸውን ይጋርዳሉ በሁለት ክንፋቸው እግራቸውን ይጋርዳሉ በሁለት ክንፋቸው ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይበራሉ፡፡ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ እያሉ ያመሰግናሉ” ኢሳ.6፡1-6፡፡

ሲበሩ ክንፋቸውን መዘርጋታቸው የመስቀል ምልክት ከመሆኑም በተጨማሪ አምላክ ሰው ሆኖ በመስቀል ተሰቅሎ ዓለምን እንደሚያድነው ምልክት ነበር፡፡
ይህን ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “በአርአያ ትዕምርተ መስቀል” በመስቀል ተሰቅለህ ዓለምን ታድናለህ ሲሉ ነው ብሎ ተርጉሞታል፡፡

መስቀል በዘመነ አበው
በዘመነ አበው መስቀል የመባረኪያ ምልክት እንደነበረ የሚያሳዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አሉ ለምሳሌ፡-
“በተአምኖ አመይመውት ያዕቆብ ባረኮሙ ለደቂቀ ዮሴፍ ለእለ አሐዱ” ያዕቆብ በሚሞትበት ጊዜ የዮሴፍን ልጆች በእምነት ባረካቸው” ዘፍ.47፡31፣ ዕብ.11፡22 “ወአስተሐለፈ እዴሁ ላዕለ ርዕሰ ኤፍሬም ወምናሴ” እጆቹን በኤፍሬምና በምሴ ላይ በመስቀል አምሳል አመሳቀለ እጆቹንም በራሳቸው ላይ ጭኖ ባረካቸው ይላል፡፡ 

ዛሬም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህኑ ቀድሶ በሚወጣበት ጊዜ በእጆቹ ይባርካል ይህም የሚያሳየው ቤተ ክርስቲያኗ መሠረቷ ከላይ በዓለመ መላእክት ከታች በዘመነ አበው ያየነው መስቀል መሆኑን ነው፡፡ “በአምስት ቀን ተኩል ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመስቀል ተሰቅዬ ሞቼ አድንሃለሁ” የሚል የተስፋ ቃል ተሰጥቷል፡፡

መስቀል በዘመነ ነቢያት እና በዘመነ ነገሥት
መስቀል በዘመነ ነቢያት በዘመነ ነገሥት እንደየሀገሩ ግእዝን /ሁኔታ/ ልዩ ልዩ ተግባራት ሲፈጽሙበት ቆይቷል፡፡ ለምሳሌ፡- ለወንጀለኞች መቅጫነት አገልግሏል በዕርግጥ አሁንም የወንጀለኞች የአጋንንት መቅጫ ነው ለሚያምኑበት ግን የጭንቅ መውጫ የነጻነት መገለጫ ነው፡፡

በተለይ ፋርስ ሰዎችን ሰቅሎ መግደል መገለጫዋ ነበር የተጀመረውም በፋርስ ነው ሰውን በመስቀል ሰቅሎ መግደል የባቢሎን እቶነ እሳት እና አናብስት፣ የሮማውሪያንና የፋርስ ስቅለት የአይሁድ ውግረት  መቅጫቸው ነው፡፡

መርዶክዮስን ሊሰቅል ባዘጋጀው መስቀል የተሰቀለው ሐማ በፋርስ ሕግ ነበር “እነሆ ሐማ ለንጉሡ በጎ ለተናገረው ለመርዶክዮስ ያዘጋጀው አምሳ ክንድ የሆነ ግንድ በሐማ ቤት ተተክሎአል “ንጉሡም በእርሱ ላይ ስቀሉት አለ ሐማንም ለመርደክዮስ ባዘጋጀው ግንድ ላይ ሰቀሉት” አስቴ.7፡9፡፡

በእርግጥም ይህን አልን እንጂ ይህ ሥርዓት ከፋርስ ወደሮማውያን ተላልፎ በመቅጫነት አገልግሎአል፡፡ አይሁድም ብዙ ጊዜ ወንጀለኞችን የሚቀጡት በውግረት በእሳት በማቃጠል ቢሆንም በመስቀልም ይቀጡ ነበር፤ ምክንያቱም መነሻው ኦሪት ነውና የኦሪት መደበኞች ደግሞ ፋርሶች ወይ ሮማውያን ሳይሆኑ እነርሱ ናቸው፡፡

“ርጉም ውእቱ ኩሉ ዘስቁል ዲበ ዕፅ” ዘዳ.21፡23 ሰርቆ ቀምቶ በእንጨት የተሰቀለ የተረገመ ይሁን” ተብሎ የተጻፈው በኦሪት ነው፡፡ ስለዚህ መስቀል የወንበዴ የሌባ መቅጫ የጥፋተኛ መቀጥቀጫ ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ ከፍተኛ ወንጀል የፈጸሙ ሰዎች አይገረፉም በመስቀል ይቀጡ ነበር፡፡ ከተገረፉ ደግሞ አይሰቀሉም፤ የፈጸሙት በደል ለዚያ ርግማን የሚያበቃ አይደለም፡፡ ማለት ነው፡፡

መስቀል በዘመነ ነቢያት በብዙ ኅብረ ትንቢት አሸብርቆ በብዙ ኅብረ አምሳል ደምቆ የመጣ እንጂ፤ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ ድንገት የተገኘ አይደለም፡፡ ለእስራኤል በ40 ዘመን ጉዟአቸው ውስጥ ተአምራት በማረግ የታዩት የሙሴ በትር እና በምድረ በዳ ሙሴ የሰቀለው አርዌ ብርት የታየበት አላማ የመስቀል ምልክቶች ወይም ምሳሌዎች ነበሩ፡፡

የሙሴ በትር ባሕር ከፍሏል ጠላት ገሏል መና አውርዷል ደመና ጋርዷል ውኃ ከአለት አፍልቋል፤ በግብጻውያን ላይ ድንቅ ድንቅ ተአምራት አድርጓል፡፡ ሙሴም ምሳሌው የሆነለት ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀልም ባሕረ እሳትን ከፍሏል ማየ ገቦን ደመ ገቦን ለመጠጣችን ለጥምቀታችን አስገኝቷል፡፡ ኃይሉን በዲያብሎስና በአጋንንት ላይ አሳይቷል፡፡ ነፍሳትን ከሲዖል ባርነት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነጻ አውጥቷል፡፡ “ወሀደፎሙ በመስቀሉ” በመስቀሉ አሻገራቸው” እንዲል መጽፈሐፈ ኪዳን፡፡ ሙሴ በምድረ በዳ የሰቀለው የነሐስ እባብ ክርስቶስ በመሰቀል የሚፈጽመውን የማዳን ሥራ የሚያሳይ ነበር፡፡

“ሙሴም ስለ ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ እግዚአብሔርም ሙሴን “የናስ እባብን ሠርተህ በዓላማ ላይ ስቀል እባቡም ሰውን ቢነድፍ የተነደፈው ሁሉ ይመልከተው ይድናልም” ሙሴም የናሱን እባብ ሠርቶ በዓላማ ላይ ሰቀለ እባቡም የነደፊችው ሁሉ የናሱን እባብ ባየ ጊዜ ዳነ” ዘኁ.21፡7፡፡

የነሐሱ እባብ የክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ የነሐሱ አባብ ጽሩይ ነው ክርስቶስም ጽሩየ ባሕርይ ነውና የነሐሱ እባብ መርዝ የለበትም ክርስቶስም መርገመ ሥነጋ መርገመ ነፍበስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የሚያድል ክፋት ተንኮል የሌለበት ነውና እባቡ የተሰቀለበት ዓላማው ደግሞ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀልምሳሌ ነበር፡፡

እባብ የነደፈው ሁሉ በተመለከተው ጊዜ ይድን እንደነበር የሰው ልጅ በሙሉ በእባብ ዲያብሎስ መርዝ ተነድፎ ቆስሎ በኃጢአት ተመርዞ ሲኖር በመስቀል በተፈጸመው የቤዛነት ሥራ ድኗልና፡፡
“ወበከመ ሙሴ ሰቀሎ ለአርዌ ምድር በገዳም ከማሁ ሀለዎ ለወልደ እጓለመሕያው ይሰቀል ከመ ኩሉ ዘየአምን ቦቱ ኢይትሐጐል አላ የሐዩ ለዓለም”

ሙሴ እባብን በምድረ በዳ እንደሰቀለው እንዲሁ የሰው ልጅ ይሰቀል ዘንድ ይገባዋል የአመነበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ዘንድ ይገባዋል” ዮሐ.3፡15፡፡

ከነቢያት ዳዊት እንዲሁም ልጁ ሰሎሞን የመስቀሉን ነገር አምልተው አጉልተው ተናግረዋል፡፡ “ወወሀብኮሙ ትዕምርተ ለእለይፈርሁከ ከመ ያምስጡ እምገፀ ቅሥት”  “ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው ወዳጆችህ እንዲድኑ” መዝ.59፡4 ለመዳን የተሰጠ ምልክት ደግሞ መስቀል ነው ለዚህ ነው እኛ ኦርቶዶክሳውያን በአንገታችን የምናስረው በእጃችን የምንይዘው የምንሳለመው የምንባረክበት ምክንያቱም የመዳን ምልክት ነውና፡፡

ጥበበኛው ሰሎሞንም የመስቀሉን ነገር በተናገረበት አንቀጽ እንዲህ ይላል “ሐረገ ወይን ኮነ መድኃኒትየ ዘእምሐሲሦን ይትገዘም ወበጎልጎታ ይተከል” “የወይን ሐረግ /መስቀል/ መድኃኒቴ ሆነ ሐሲሦን ከተባለ ቦታ ይቆረጣል በጎልጎታ ይተከላል” መኃ.3፡44 ግዕዙን ተመልከት፡፡

ዳዊት ለመዳን የተሰጠ መሆኑን ሲገልጽ ልጁ እንጨቱ ከየት ተነቅሎ በየት ቦታ እንደሚተከል እና መድኃኒትነቱን አጉልቶታል ስለዚህ መስቀል በብሉይ ኪዳን ትልቅ ቦታ ይዟል ማለት ነው፡፡
መስቀል በሐዲስ ኪዳን

መስቀል ከብሉይ ኪዳን ይልቅ የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ ቅድስና ያለው ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበትም ሰው ከውድቀቱ የተነሳበት መሆኑ ተረጋጋጧል፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን ጌታችን የተሰቀለበት መስቀል የተዘጋጀው ከሰባት ዓይነት ዕፅዋት ነው፡፡
1.    ሳኦል ከገነት ያስመጣው ዕፅ
2.    ሰሎሞን ቤተ መቅደስን በሠራበት ወቅት ሠረገላ አድርጎ የተጠቀመበት ዕፅ
3.    ከመቃብረ አዳም የበቀለ ፅፀ ሕይወት
4.    ሎጥ በእንባው ያለመለመው ፅፀ ከርካዕ
5.    ታቦተ ጽዮንን ይሸከሙበት የነበረው ሠረገላ
6.    ጌታችን በቢታንያ የረገማት ዕፀ በለስ
7.    ዘኬዎስ ጌታችንን ለማየት የወጣበት ዕፀ ሠግለ /ሾላ/ ከእነዚህ ሰባት ዕፅዋት በተዘጋጀ መስቀል ነው ጌታችን የተሰቀለው /መጽሐፈ ኪዳን ትርጓሜ ተመልከት/ 

ጌታችን ከእነዚህ ዕፅዋት የተዘጋጀ መስቀሉን ተሸክሞ በቀራንዮ አደባባይ በመስቀሉ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ ቀድሶታል በዚህ የተነሣ መስቀል ነዋይ ቅዱስ ነው መስቀል በሐዲስ ኪዳን ሁለት መሠረታዊ ትርጉሞች አሉት፡፡
1.    ጌታችን የተሰቀለበት ከሰባት ዕፅዋት የተዘጋጀውን መስቀለኛ እንጨት /ቅዱስ መስቀል/
2.    ጌታችን ዓለምን ለማዳን የተቀበለው መከራ መስቀል ይባላል መስቀል ስንል እነዚህን ከላይ ያነሳናቸውን ሁለት አበይት ትርጉሞች ማስታወስ የግድ ይላል፡፡
 የመስቀሉ በረከት ይደርብን!

No comments:

Post a Comment