Showing posts with label ዐውደ_ስብከት. Show all posts
Showing posts with label ዐውደ_ስብከት. Show all posts

Friday, December 16, 2016


              

     ሕልመ ሌሊት
 በጠለቀ
እንቅልፍ ላይ ሳሉ የሚከሠት ሕልመ ሌሊትን እንደ ኃጢአት እንዲቆጠርና እንዳይቆጠር የሚያደርጉ የተለያዩ ሁኔታዎች አሉ:: ስለዚህ ሕልመ ሌሊትን በጥቅሉ ኀጢአት ነው ወይም አይደለም ማለት አይቻልም:: ነገር ግን እንደ ኀጢአት እንዲቆጠር የሚያደርጉ ሁኔታዎችን በመጠኑ መዘርዘር ይቻላል::
/. አጋንንት የሰውን ልጅ በተኛበት ክፉ ክፉ ሕልም በማሳየት ይፈትኑታል:: አንድ ጊዜ የተራቆተ የሴት ገላ; በሌላ ጊዜ ደግሞ እንደ ወንድና ሴት አለሌና ባዝራ እየሆኑ ሲጨዋወቱና ሲደራረጉ በምትሐት ያሳዩታል:: በዚህ ጊዜ እርሱም በዝሙት ሐሳብ ይሳብና በሕልሙ ዝሙት ሲፈጽም ያድራል:: በዚህ መልኩ የተከሠተ ሕልመ ሌሊት "ጸዋግ" ወይም "ኅሡም" ሕልም ይባላል:: ክፉ
ወይም ጥፉ ሕልም ማለት ነው::
በዚህ መልኩ አጋንንት ሰውን እንደሚዋጉት
በመጽሐፈ መነኮሳት እንዲህ ተጽፏል:: "ይትቃተልዎ ሰይጣናት በመዓልት
በሕሊናት እኩያት ወበሌሊት በአሕላማት ኅሡማት" በአማርኛ "ሰይጣናት
የሰውን ልጅ ቀን ቀን ክፉ ሐሳብ በማሳሰብና በማሠራት በሌሊት ደግሞ ዝሙት የሞላበት አስጸያፊ ሕልም በማሳየት ይዋጉታል"

Thursday, March 10, 2016

አርጋኖን

የመዝሙር መሳሪያዎች በተነሳ ቁጥር ይሄ አርጋኖን የተሰኘ የዜማ እቃ በቤተክርስቲያን አባቶችና አንዳንድ ሰዎች ዘንድ ልዩነት እየፈጠረ እስከአሁን ቆይቷል፡፡ በቅርቡ የአሜሪካው "ሲኖዶስ" ዋና ጸሐፊ የሆኑት አቡነ መልከጼዴቅ አርጋኖን/ኦርጋን ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የምስጋና ዕቃ እንዲሆን  አውጀዋል፡፡ እንዲህ ነው አንዲያ ነው ከማለት በፊት የአርጋኖንን ጥነተ ነገሩን ጥንተ መሠረቱን መመርመር ተገቢ ነው፡፡

ኦርጋኖንአርጋኖን የግሪክ ቃል ሲሆን ጥሬ ትርጉሙ መሣርያ ማለት ነው፡፡ ጥንታዊው የግሪክ ፈላስፋ አሪስቶትል (አሪስጣጣሊስ) ኦርጋኖን የሚለውን ቃል የስነ አመክንዮ መሳሪያ ወይም የሐሳብ መግለጫ መንገድ ዘዴ በማለት ቃሉን ተጠቅሞታል፡፡ነገር ግን በ3ኛው መ/ክፍለ ዘመን ቅ.ል.ክ ክቲሲቢዮስ ዘእስክንድርያ የተባለ ግሪካዊ ተመራማሪና መሐንዲስ ሃይድሮሊስ (የውሃ ኦርጋን) የተሰኘ የዜማ መሣሪያ ከፈለሰፈ በኋላ ኦርጋኖን የሚለው ቃል የዜማ ዕቃ/መሣሪያ የሚለውን ትርጉም ጨምሮ ወርሷል፡፡ ይህ የሙዚቃ መሣርያ በጥንት ዘመን የአደባባይ መዝናኛ በዓላት ማድመቂያ በመሆን በሰፊው  አገልግሎት ይሰጥ እንደነበር በታሪክ መጻሕፍት ተመዝግቧል፡፡ በተደረጉ የአርኪዮሎጂካል ቆፋሮዎችም ይህ ሁለት ሺህ ሦስት መቶ አመት ገደማ ያስቆጠረ ጥንታዊ መሳሪያ ከተቀበረበት ወጥቶ በአውሮፓ ሙዚየሞች ለእይታ በቅቷል፡፡ ነገር ግን ከ 5ኛው ክፍለ ዘመን ድ.ል.ክ በኋላ ተቀባይነቱ ቀንሶ በሌሎች እርሱን መሰል የተሻሻሉ መሳሪያዎች (ፓይፕ ኦርጋን፣ ሪድ ኦርጋን፣ ቸርች ኦርጋን) ተተክቷል፡፡ ይህ ሃይድሮሊስ ወይም ኦርጋኖን የተባለ የዜማ መሣሪያ አሁን ኦርጋን ለተሰኙት ባለቁልፍ ሙዚቃ መሣሪያዎች ቅድመ አያታቸው ነው፡፡ ስለዚህ ኦርጋኖን/አርጋኖን በዘመናችን ኦርጋን የሚለው ቃል ይተካዋል፡፡ አርጋኖንን በገና ብለው የተረጎሙ አሉ፡፡ ይህ ማለት ግን አርጋኖን በገና ነው አያሰኝም፡፡በገና የክር መሰሪያ ሲሆን አርጋኖን ደግሞ ከቁልፍ መሣሪያዎች ጎራ የሚመደብ ነው፡፡ አርጋኖን ኦርጋን አደለም ብሎ መሟገትም አያዋጣም፡፡

እንግዲህ ስለ አርጋኖን አመጣጥ ይህን ካልን፡፡ ሊቃውንት ቤተክርስቲያን ስለ አርጋኖን ምን እንዳሉ እንመልከት፡፡ አርጋኖን የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድ በዜማ ድርሰቶቹ ጠቅሶታል፡፡
ሰባኬ ወንጌል ዮሐንስ አርጋኖነ ትንቢት ዘይደምጽ ለቤተ ክርስቲያን…ወንጌልን የምትሰብክ ዮሐንስ ለቤተክርስቲያን ሰናይ ድምጽን የምታሰማ የትንቢት አርጋኖን ነህ በማለት ቅዱስ ያሬድ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድን በድጓው አወድሷል፡፡ በተጨማሪም በማክሰኞ አርያሙ  ከመ ዝብጠተ መሰንቆ አርጋኖን ስብሐቶሙ ለእሙንቱ ካህናት…የካህናቱ ምስጋና መሰንቆ አርጋኖን ሲመታ እንደሚያወጣው ሰናይ ድምጽ ጣፋጭ ነው ባሏል፡፡

ቅዱስ ያሬድ የካህናትን ጥዑም ድምጽ፣ የሐዋርያትን ስብከት ከአርጋኖን ጋር መስሎ  ይህን ሲል በሁለት መንገድ ልንተነትነው እነችላለን፡፡  አንደኛው  አርጋኖን የሰኘውን የዜማ መሣሪያ ቅዱስ ያሬድ በነበረበት ወቅት አገልግሎት ላይ ስለነበር የመሣሪያውን መልክና ቁመና እንዲሁም ድምጹን ያውቀዋል፤ ሁለተኛው  ደግሞ ቅዱስ ያሬድ ከመጻሕፍት አግኝቶ ለድርሰቱ ውበት ተጠቅሞታል፡፡ ያም ሆነ ይህ አርጋኖን የተባለውን የዜማ መሣርያ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ከመሰንቆ፤ ከእንዚራ ጋር አስተባብሮ ቅዱሳንን ለማመስገን መስሎ አቅርቦታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በነበረበት ዘመን አርጋኖን አግልግሎት ላይ ነበር ለማለት ይቻላል፡፡ እንዲያውም ቅዱስ ያሬድ ለመጀመሪያ ጊዜ ዜማን ሲደርስ ወደ አርያም ተነጥቆ ካያቸውና ከሰማቸው  የዜማ ዕቃዎች አንዱ ኦርጋኖን/ኦርጋን እንደነበር ገድለ ያሬድ ይተርካል፡፡

ወሰምዐ በህየ ቃለ እንዚራ ወቃለ አርጋኖን ወቃለ መሰናቅው እንዘ ይሴብሕዎ ወይዌድስዎ ወየአኵትዎ ለፈጣሬ ሰማያት ወምድር በስብሐት ወበማኅሌት…በዚያም የእንዚራን፣ የአርጋኖንን፣ የመሰንቆን እንዲሁም ሰማይና ምድርን የፈጠረ እግዚአብሔርን በስብሐትና በማኅሌት ሲያመሰግኑት ሰማ፡፡

አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም የቅዱስ ያሬድን የምስጋና ፈለግ ተከትሎ እመቤታችንን በአርጋኖን በመመሰል ብዙ የውዳሴ ድርሰቶችን ለቤተክርስቲያን አበርክቷል፡፡

እንግዲህ ሊቃውንቱ አርጋኖንን እንደ ምሳሌ ከመጠቀም ያለፈ ነገር አልተናገሩም፡፡ የኢትዮጽያ ቤተክርስቲያን አባቶችም ይህ አርጋኖን የተሰኘ የዜማ እቃን ተጠቅመው ሲያመሰግኑ በታሪክ ተመዝግቦ አላገኘንም፡፡ ሆኖም በኦርጋን የሚደርስ ምስጋና የረከሰ እግዚአብሔር የማይቀበለው፤ በዋሽንትና ክራር የሚደረግ ግን የተቀደሰና እግዚአብሔር የሚቀበለው እንደሆነ አድርጎ ማሰብ ግን የተሳሳተ ነው፡፡ መቃወማችን እግዚአብሔር በአርጋኖን/ኦርጋን አይመሰገንም ከሆነ ተሳስተናል፡፡ ምክንያቱም የዜማ ዕቃዎች ሁሉ ሰው ሰራሽ ናቸው፡፡ ከሰማይ የወረደ በገና፤ ከሰማይ የወረደ ከበሮ፤ ከሰማይ የወረደ መሰንቆ የለንም፡፡ ኦርጋንን የሰራው ሰው ነው  በገናውም የሰው ፈጠራ ነው ያውም የመጀመሪያ አላማው ለዘፈን ነበር ዘፍ. 4፡ 21 ፡፡ ዋሽንቱም ብትሉ ጣዖት ማጀቢያ እንደነበር በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፏል ዳን 3፡ 5-7፡፡ ሰው ባለው ባገኘው እንደየባሕሉ ማመስገን ይችላል፡፡ለሰይጣን ንብረት የለውም፡፡ ቁም ነገሩ አጠቃቀማችን ላይ ነው፡፡ ግዴታ በመሰንቆና ዋሽንት ካልሆነ አይባልም፡፡ እግዚአብሔር በከበሮና ጸናጽል በክራርና ዋሽንት ብቻ ካላመሰገናችሁኝ አልቀበልም አላለም፡፡  

ኧረ ለመሆኑ ክራርና ቤስ ክራር እያቀላቀሉ በያሬዳዊ መዝሙር ስም ጆሯችንን ያደነቆሩት ዘማሪዎቻችንን አሜን ብለን ተቀብለን ይኸው በየታክሲው በየመዝሙር ቤቱና በየመሸታ ቤቱ ስናስጮቸው አይደል የምንውለው? የሲኖዶሱ ቀኖናስ ከተሻረ አልሰነበተም ወይ? በየትኛው የሲኖዶስ ጉባዔ ወይም በየትኛው ሐዋርያዊ ቀኖና ነው ክራርና ቤዝ ክራር የመዝሙር መገልገያ ዕቃ ሁነው የተመዘገቡት? አቡነ መልከጼዴቅ በዚህ ነገር ልክ ብለዋል፡፡ ክራሩን ተቀብለን የኦርጋን ነገር ሲነሳ የሚያስነጥሰን ከሆነ ችግር ነው፡፡

ነገር ግን ይህን ሲባል ኦርጋን ቤተክርስያናችን ይግባ ለማለት አይደለም፡፡ ይህን መወሰን የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶሱ ብቻ ነው፡፡ ዲያቆን እገሌ፣ ቄስ እገሌ መምህር እገሌ ስለተናገረ የሚሆን ነገር የለም፡፡ ስልጣኑ የቅዱስ ሲኖዶሱ እና የቅዱስ ሲኖዶሱ ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም በኦርጋን እንድናመሰግን አልፈቀደም፡፡ በተጨማሪም ቤተክርስቲያን ኦርጋንና ሌሎች ዘመነኛ የዜማ ዕቃዎች አያስፈልጓትም፡፡ ያሉት የዜማ ዕቃዎች በቂ ናችው፡፡  ስለዚህ ስርአተ ቤተ ክርስቲያንን ከማስጠበቅ አንጻርና ወደፊት ኦርጋንን ተከትሎ ከሚመጣ ስርአት አልበኝነትና ጋጠወጥነትን እስቀድሞ ከመከላከል ረገድ ኦርጋንና ሌሎች ዘመናዊ የዜማ መሣሪያዎችን ከቤተክርስቲያን ማራቁ ተገቢ ነው፡፡

ሐዋርያት በየትኛውም የዜማ መሳሪያ ተጠቅመው ሲያመሰግኑ አልተመዘገበም፡፡ በዘመነ አበው የነበሩ እነ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ አውሳቢዮስን የመሰሉ  ታላላቅ የቤተክርስቲያን አባቶችም የዜማ መሳሪያን ተጠቅመን የአምልኮ ሥርዓት እንድንፈፅም አላዘዘኑም አላስተማሩንምም፡፡ እንዲያውም በተቃራኒው የሐዲስ ኪዳን አማኝ የሆንን እኛ ክርስቲያኖች ከዜማ መሳሪዎች ርቀን በልባችን እንዚራ በአንደበታችን መሰንቆ ብቻ ማመስገን እንደሚገባን ሰብከዋል፡፡


ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

Friday, September 25, 2015

መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ

  በቅmeskel dameraድሚያ ከዘመን ወደ ዘመን ያሸጋገረን ለብርሃነ መስቀሉ ያደረሰን በሀብቱ የሳበን በረድኤቱም ያቀረበን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፡፡

ከላይ በርዕሱ ያነሣነው ኃይለ ቃል ቅዱስ አትናቴዎስ የመስቀሉን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ የተናገረው ነው፡፡ አስተሀፈረ ኃጢአተ በዲበ ምድር ወሰአረ መርገመ በዲበ ዕፀ መስቀል ወአብጠለ ሞተ በውስተ ሲዖል ወነሰተ ሙስና እምውስተ መቃብር”

“በምድር ላይ ኃጢአትን አሳፈረ መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ ሞተ ነፍስን በሲዖል አጠፋ ፈርሶ በስብሶ መቅረትን በመቃብር አፈራረሰ” በማለት ጌታችን ለሰው ልጆች ነጻነት እና ድኅነት የከፈለውን የቤዛነት ሥራ በተናገረበት ክፍል የተናገረው ነው የሰው ልጆች ነጻነታቸው የተዋጀው በመስቀል ተሰቅሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በሥልጣኑ ለይቶ ዲያብሎስን በመስቀሉ ገሎ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ወርዶ ነፍሳትን ከዲያብሎስ ባርነት ከአጋንንት ቁራኝነት ከሲዖል ግዛት ነጻ አውጥቷቸዋልና፡፡

Wednesday, September 23, 2015

ተቀጸል ጽጌ- የዐፄ መስቀል


 ተቀጸል ጽጌ ማለት የአበባ በዓል ማለት ነው፡፡ ክረምቱ፣ ድጡ፣ ማጡ፣ ችግሩና ጨለማው ተወግዶ ምድር በልምላሜ የምታሸበርቅበት፣ በአበባ የምትደምቅበት ወቅት በመሆኑተቀጸል ጽጌ እየተባለ ይከበራል፡፡የተቀጸል ጽጌ በዓል የተጀመረው በ6ኛው ምዕተ ዓመት በዐፄ ገብረ መስቀል አማካይነት ሲሆን በዓሉ የሚከበረው የክረምቱ ማብቃት የሚያበስሩ አበቦች በሚፈኩበት ወር በመስከረም 25 ቀን ለንጉሡ የአበባ ጉንጉን /አክሊል/ በማበርከት ነበር፡፡

Tuesday, August 4, 2015

ጾመ ፍልሰታ ለቤተ ክርስቲያን ሰላም


ኢትዮጵያ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአሥራት አገር ናት፡፡ ሊቃውንትም ነቢያት የተነበዩትን ትንቢት የቆጠሩትን ሱባዔ መሠረት በማድረግ ቅድስት ድንግል ማርያም በኪደተ እግሯ ኢትዮጵያን መባረኳን ያስተምራሉ፡፡ «ነቢዩ ዕንባቆም የኢትዮጵያ ድኳኖች ሲጨነቁ ዐየሁ፤» ዕንባ. 37 ብሎ የተናገረው ቃለ ትንቢት እመቤታችን የኢትዮጵያን አውራጃዎች ለመባረኳ ማስረጃ መሆኑን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይተረጉማሉ፤ ያመሠጥራሉ፡፡
 
ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን ለእናቱ አሥራት አድርጐ በመሥጠቱ በእርሷ በኩል ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሆን የነገረ ድኅነት ምሥጢር በመከናወኑ ኢትዮጵያውያን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተለየ ፍቅር አለን፡፡ የአብነት /የቆሎ/ ተማሪዎች በትምህርት ዓለም ከአንዱ ወደሌላው እየተዘዋወሩ /የአብነት/ ትምህርት ሲማሩ በእንተ ስማ ለማርያም፤ ስለማርያም እያሉ፡፡ የእመቤታችን ስም ስንቅ ምግብ ሆኗቸው ይጠቀሙበታል፡፡ ግሼን ደብረ ከርቤ የልጇ ግማደ መስቀል ከከተመበት አምባም የሚጓዙ ምእመናን «አንድ እፍኝ ሽምብራ አልያዝኩም ከቤቴ ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ» እያሉ በፍቅሯ ተማርከው ግብር ሰፍረው ዕጣን ቋጥረው ሱባዔ እየገቡ ይማፀኗታል፡፡

Saturday, July 11, 2015



ሰማዕተ ጽድቅ ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ

  እነዚህ ሁለት ቅዱሳን አባቶቻችን የቅድስት ቤተክርስቲያናችን አዕማድ ናቸው፡፡ በመሠረትነት በአጸኗት ቤተክርስቲያን ያላቸው የክብር ሥፍራ ላቅ
ያለ ነው፡፡ ይህ የሆነው እንዲሁ አይደለም፡፡ ለቤተክርስቲያንና
በቤተክርስቲያን የፈጸሙት አገልግሎት በዚህም የተቀበሉት ሰማዕትነት
ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህን መልካም የሆነውን ታሪካቸውን ለእኛ
አርአያነት በሚሆን መልኩ ከትበውልናል፡፡ እኛም ለአርአርያነት በሚሆን
መልኩ የእነዚህን ደጋግ ሁለት ቅዱሳን አባቶች ታሪክ፣ ዕውቀትና
መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ከዚህ በመቀጠል አቅርበናል፡፡
1. ሁለቱ ሐዋርያት ሲጠሩ የነበሩበት ሕይወት
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በገሊላ ባሕር ዳር በምትገኘው በቤተ ሳይዳ
ሲወለድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ በጠርሴስ ከተማ ተወለደ፡፡

Tuesday, June 30, 2015

ጸሎተ ፍትሐት ምንድ ነው? ለምንስ ይጠቅማል?
 

 
ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም.
ፍትሐት ማለት ከዚህ ዓለም በሞት ለሚለዩ ሰዎች በሕይወተ ሥጋ ሳሉ ከሠሩትና ከፈጸሙት በደል እንዲነጹ ከማእሠረ ኃጢአት እንዲፈቱ ወደ እግዚአብሔር የሚቀብ ጸሎት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሙታን ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግ ታዝዛለች፡፡
ጸሎተ ፍትሐት ለበደሉት ሥርየት ኃጢአትን፣ ይቅርታን ዕረፍተ ነፍስን ያሰጣል፡፡ ለደጋጎች ደግሞ ክብርን፣ ተድላን፣ ዕረፍትን ያስገኛል፡፡

Friday, May 29, 2015

                                የእግዚአብሔርን ስም በከንቱ አትጥራ!

የእግዚአብሔርን ስም በከንቱ መጥራት ሲባል ምን ማለት ነው? የአምላካችን የእግዚአብሔር ስም የከበረ በመሆኑ እንደተገኘ የሚጠሩት፣ እንደአጋጠመ የሚናገሩት አይደለም፡፡ ይልቁንም በመፍራትና በመንቀጥቀጥ በትሕትና ሆነው ሊጠሩት የሚገባ ክቡር ስም ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ሰዎች የእግዚአብሔርን ስም ያለአግባብ በነገራቸው ሁሉ ውስጥ ሲያስገቡት፣ ሥፍራም ጊዜም ሳይመርጡ እንደፈለጉት ሲጠሩት ይስተዋላሉ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች እምነትና ፊሪሃ እግዚአብሔር አላቸው ለማለት አያስደፍርም፤ ምክንያቱም የሚያምኑና
 
ከዚህ ቀጥለን ሰዎች ስሙን በከንቱ የሚጠሩባቸውን ሁኔታዎች ባጭር ባጭሩ ለመመልከት እንሞክራለን፡፡

Wednesday, May 20, 2015

ዕርገተ ክርስቶስ

ግንቦት12ቀን 2007ዓ.ም
በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ
አልቦ ዘዓርገ ውስተ ሰማይ ዘእንበለ ዘወረደ እምሰማይ ወልደ ዕጓለመሕያው ዮሐ.3፥13
Ereget
ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡ እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው፡፡ ይህ ኃይለ ቃል ክብር ምስጋና ይግባውና ስለጌታችን፣ አምላካችን፣ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት መውረድ ከድንግል ማርያም መወለድ እና የሰውነቱን ሥራ ጨርሶ በክብር ወደ ሰማይ ማረጉን የሚገልጽ ነው፡፡ እንደሚታወቀው አምላካችን ስለሁለት ዐቢይ ጉዳዮች ሰው ሆኗል፡፡

Wednesday, May 6, 2015

ስለትያትርና ኪነጥበብ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እነዳስተማረው

ከአቤል ተስፋዬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
…እንግዲህ (አብዝታችሁ) ብታነቡ የጌታችን ተከታይ ሆናችኋል፡፡ እርሱም ያነባ (ያለቅስ) ነበርና፤ በአልአዛር (መቃብር ላይ)፤ በከተማይቱ (ኢየሩሳሌምን) ላይ፤ ይሁዳም ባገኘው ጊዜ አብዝቶ አዝኖ ነበር፡፡ ብዙዎች ሲያዝን አይተውታል ነገር ግን ሲስቅም ሆነ ፈገግ ሲል ለቅጽበት ስንኳ በየትኛውም ጊዜ ያየው አንዳችም የለም፤ ከወንጌላውያኑ የትኛቸውም ይህን እንዳደረገ አልገለጹም፡፡ (ቅ.) ጳውሎስንም እንዲሁ፤ እንዳለቀሰ፤ ለሶስት አመታት ቀን ከሌሊት (ያለመቋረጥ) እንዳነባ ራሱም ገልጿል፤ ሌሎችም ስለርሱ ይህን መስክረዋል፤ እንደሳቀ ግን እርሱም የትም ቦታ ላይ አልጠቀሰም ከሌሎች ቅዱሳንም መካከል ይህን እንዳደረገ የተገለጸ ማንም የለም፤ ስለ ሳራ (የአብርሀም ሚስት) (እንደሳቀች) ተጠቅሷል ይኸውም (በሦስቱ መላዕክት) በተገሰጸችበት ወቅት ነበር፤ እንዲሁም የኖኸ ልጅ በተመሳሳይ ስለመሳቁ ተጽፏል፤ ይህን ባደረገበት ወቅት ግን (በአባቱ ተረግሟልና) ነጻነቱን በባርነት ለወጠ፡፡

እንዲህ የምላችሁ ሳቅ (ጨዋታ) የተባለን ሁሉ ለመኮነን አይደለም፤ አእምሯችሁ በከንቱነት እንዳይጠመድ ለማቀብ ነው እንጂ፤ እስኪ ልጠይቃችሁ በምቾት የምትንደላቀቁና በከንቱነት የተዘፈቃችሁ ሆናችሁ ሳለ በሚያስፈራው (የጌታችን) የፍርድ መንበር ፊት ቆማችሁ እዚህ (በምድር) ላይ ሳላችሁ ስለሰራችሁት ነገር አንድ በአንድ አትጠየቁምን? በእርግጥ እንጂ… ምክንያቱም አውቀን በድፍረት ስለሰራነውም ሆነ ከአቅማችን በላይ ሆኖብን ስለበደልነው በደል ምላሽ እንድንሰጥ እንጠየቃለንና… ‹‹ በሰዎች ፊት የሚክደኝን ሁሉ እኔ ደግሞ (በሰማዩ) አባቴ ፊት እክደዋለሁ›› ይላልና ጌታ፡፡ አለጥርጥር ማናችንም ጌታን ወደን አንክደውምና አውቀንና ፈቅደን አናደርገውም፤ ነገር ግን ይህም ቢሆን ከቅጣት አያድነንምና ይህንንም አስመልክቶ መልስ መስጠት ይኖርብናል፤ አውቀን ስለሰራነው ብቻ ሳይሆን ሳናውቅ የበደልነውም ጭምር ያስጠይቀናል፡፡ ‹‹ በራሴ አንዳች አላውቅም፤ ነገር ግን ይህ ምክንያት ሆኖኝ ከፍርድ አላመልጥም (አልድንም)›› ይላልና 1 ቆሮ 4፡4 ፤ደግሞም በሌላ ስፍራ እንዲህ ይላል ‹‹ ለእግዚአብሔር ቀናኢነት ያላቸው ናቸውና ይህን ቆጥሬላቸዋለሁ፤ ነገር ግን በእውቀት አይደለም›› ይሁን እንጂ ይህ በቂ ምክንያት ሆኖ አልተገኘም፡፡ ወደ ቆሮንጦስ ሰዎች በጻፈበት ወቅትም ደግሞ (ሐዋ. ቅ. ጳውሎስ) እንዲህ ብሏል ‹‹ እባቡ ሔዋንን በረቂቅ ተንኮሉ እንዳሳታት ሁሉ በጌታችን ካለ ቅንነት አእምሯችሁን እንዳይበርዘው እፈራለሁ››

Saturday, March 28, 2015

፯ተኛ ሳምንት ኒቆዲሞስ




ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የሆነ የአይሁድ አለቃ እና መምህር ነበረ “ወሀሎ አሐዱ ብእሲ እምፈሪሳውያን ዘስሙ ኒቆዲሞስ መልአኮሙ ለአይሁድ” ዮሐ3÷1 እንዲል፡፡ ሳምንቱ (ሰንበቱ) በእርሱ የተሰየመበት ዋናው ምክንያት ይህ ሰው በሌሊት እየመጣ ምስጢረ ጥምቀትን፣ ዳግም ልደትን ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ እግር ስር ቁጭ ብሎ የተማረበት ቀን መታሰቢያ ስለሆነ ነው፡፡ በዚህም ትምህርቱ ጌታችን ዋና የሆነውን እና ሰው ከውሀ እና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግስት እንደማይገባ በግልጽ አስተምሮታል፡


ኒቆዲሞስ ከቀን ይልቅ በሌሊት መማርን ስለምን መረጠ? 


ኒቆዲሞስ ይህንን ያደረገው ስለሶስት ነገር እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ይናገራሉ ያስተምራሉ፡፡

Saturday, March 21, 2015

፮ተኛ ሳምንት ገብርኄር



ገብርኄር ማለት ቸር አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ይህንንም  በ ማቴ 25 ፥ 14-30 ላይ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የወንጌልን አደራ በምሳሌ እንዳስተማረ እንረዳለን፡፡ ትምህርቱ አንድ ባለጸጋ ሰው ነበረ ወደሩቅ ሀገር ለመሄድ ባሰበ ጊዜ አገልጋዮቹን ጠርቶ ከመንገዱ እስኪመለስ ድረስ ይሰራለት ዘንድ ለአንዱ አምስት፣ ለሁለተኛው ሁለት፣ ለሶስተኛው አንድ መክሊት (ታለንት) ሰጣቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት መክሊት በማትረፍ አስር መክሊት አደረገው፤ ሁለት መክሊት የተቀበለው  ወጥቶ ወርዶ እጥፍ አትርፎ  አራት አደረገው፡፡ ባለ አንዱ ግን ወደ ስራ ከመግባቱ በፊት በልቡ ውስጥ ስጋት፣ ጥርጣሬ፣ ፍርሀትንና አለማመንን ስላነገሰ ብሰራበት ቢጠፋብኝስ? ቢሰርቁኝስ? ቢቀሙኝስ? እያለ በማሰብ እሰራለሁ ብዬ ያለኝን ከማጣ ለምን ደብቄ  አስቀምጬ በመቆየት ሲመጣ የሰጠኝን አልመልስም ብሎ መክሊቱን  ቆፍሮ ቀበረው፡፡ ጊዜው ሲደርስ ባለንብረቱ መጣና አገልጋዮቹን ይተሳሰባቸው ጀመር፡፡

መጾም

ብጹዕ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ እነዳስተማሩት
ከዲን. በረከት ሐጎስ

ጾምን ጹመው የጾምን በረከት የማያገኙ ከጾም ጥቅምም የማይካፈሉ በከንቱ ይጾማሉ፡፡
ወርኃ ጾም የጥልቅ መንፈሳዊ ልምምድ ጊዜ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት ለእግዚአብሔር ያለንን ታላቅ ፍቅር የምናስመሰክርበት ወቅት ነው፡፡ ከዚህ ጥልቅ ፍቅረ እግዚአብሔር የተነሳ አንድ ጿሚ በስጋዊ አካሉ ላይ ይሰለጥናል፡፡ ከምድራዊ ምኞቶችና ስስቶች በላይ ይንሳፈፋል፡፡ ሰማይዊውን ያጣጥማል፡፡ ጾም ወደ አምላካችን የምንቀርብበት፣የምናውቅበት ብሎም ሰውነታችንን ስለ እግዚአብሔር የምንቀድስበት ዘመን ነው፡፡ ጾም የነፍስ እረፍት፤ የመንፈስ እርካታ የምናገኝበት ዲያቢሎስንም የምንዋጋበት የተቀደሰ ጊዜ ነው፡፡

የጾም ጊዜያት ከወትሮው በተለየ መልኩ ለመንፈሳዊ ኃይል የተሰጡ ናቸው፡፡ ገበሬ በመኸር ወራት አዘመራውን ሰብስቦ ከፊሉን ለገበያ ከፊሉን ለወርኃ ክረምት መቆያ እንደሚያከማች ሁሉ ክርስቲያኖችም በወርኃ ጾም በድካምና ጻማ የሚዘሩትን መንፈሳዊ አዝመራ የሚሰበስቡበት ወቅት ነው፡፡ የሚጾም ሰው በጾም ወራት መንፈሳዊ ኃይልና ብርታትን ከአምላኩ ይቀበላል፡፡   በእነዚህ የተቀደሱ ወራት የሚጎናጸፈው ኃይልም በፍስግ ቀናት ምርጉዝ ፣ ምቅዋም ይሆነዋል፡፡

Saturday, March 14, 2015

ደብረ ዘይት




ደብረ ዘይት ማለት የወይራ ዛፍ የበዛበት ተራራ ማለት ነው፡፡ ከኢየሩሳሌም በስተምስራቅ እንደምትገኝ ይነገራል፡፡ በዚህች ተራራ ሐዋርያት ስለ ዳግም ምጽአት ፣ ስለ ዓለም ህልፈት መቼና እንዴት እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጌታን ጠይቀውታል፡፡ የዘመኑ ፍፃሜ ሲቀርብ የሚታዩትን ምልክቶች በዝርዝር ነግሯቸዋል፡፡ (ማቴ 24 ፥ 1) በዚህ ሰንበትም ይህ ታሪክ የሚዘከርበት በመሆኑ ሳምንቱ በተራራው ስም ተሰይሟል፡፡

እንግዲህ በብሉይ ኪዳን  ዘመን ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ከአቤሴሎም በሸሸ ጊዜ የደብረ ዘይትን ተራራ ዐቀበት እንደወጣ (2ኛሳሙ 15 ፥ 30) ላይ እናነባለን፡፡ቤተ ፋጌና ቢታንያ የሚባሉት ታሪካውያን ቦታዎች ከደብረ ዘይት ግርጌ ይገኛሉ፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሆሳዕና ዕለት ከደብረ ዘይት ወደ ኢየሩሳሌም እንደ ገባ እናነባለን፡፡ ጌቴሴማኒ የሚባለው ጌታችን የጸለየበት ቦታ ከደብረ ዘይት ስር ይገኛል፡፡(ማቴ 26 ፥ 30-36) ጌታችን ወደ ሰማይ ያረገው በደብረ ዘይት ላይ ነው(ሉቃ 24 ፥ 1-52 ፣ ግ.ሐዋ 1 ፥ 12)፡፡ እግዲህ እነዚህ ሁሉ በቅዱስ መጽሐፍ ስለ ደብረ ዘይት የተነገሩ ናቸው፡፡ 

Friday, February 27, 2015

መባከን በመንፈሳዊ አገልግሎት


መንፈሳዊ አገልግሎት ሲባል ሁሌም የምትታወሰው ቤተ-ክርስቲያን ናት፡፡ይህ አገልግሎት የቤተ ክርስቲያንን ህይወት በእጅጉ የተንተራሰ  ሠፊ የቅድስና መንገድ ነው፡፡ከዚህ ህይወት የምንረዳው አንዱና ትልቁ ነገር የቤተ ክርስቲያን ህይወት የተጋድሎ ህይወት መሆኑን ነው፡፡ይህ ትግልም ለግል ክብርና ዝና ወይም እንደ ህልም ታይቶ ለሚጠፋው ለዚህ ዓለም ሥልጣን እና ምቾት ሳይሆን በስጋ የተገለጠው እግዚአብሔር ወልድ የገለጠውን የመዳን ምስጢርና እውነት ለመመስከርና ይህን የእውነት ቃል ለሰዎች ለማዳረስ የሚደረግ ተጋድሎ ነው፡፡

እንግዲህ በዚህ ህይወት ውስጥ ብዙ ተቃራኒዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ዛሬ ማንሳት የፈለግነው ስለተቃራኒ ፈተናዎች ሳይሆን መንፈሳዊ አገልግሎት ራሱ የዲያብሎስ የቅንብር ስራ ሊሆን እንደሚችል እና ብዙዎቻችን በዚህ መንፈሳዊ መሰል አገልግሎት ተጉዘን ፍጻሜያችን ግን ምን ሊሆን እንደሚችል እንመለከታለን፡፡ዲያብሎስ የሰውን ልጆች ከጽድቅ መንገድ ማራቅ የተለመደ ስራው ነው፡፡ የሰው ልጆች ዕለት ዕለት ወደ አምልካቸው ወደ እግዚአብሔር በሚያደርጉት የቅድስና ጉዞ እንቅፋት በመሆንም ሊያገኙት ከነበረው ክብር እና ጸጋ ፈጽሞ እንዲለዩ ያደርጋል፡፡እንግዲህ ይህንን ተግባሩን በተለያዩ መንገዶች እና ስልታዊ በሆኑ ዕቅዶች ያከናውናቸዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ተስፋ በማስቆረጥ፣ጥርጣሬ በመትከል፣በማዘግየት፣መልካም ምግባራትን

Tuesday, February 24, 2015

መንፈሳዊት ፍቅር


   ልዑል እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ከልዕልና ወደ ትህትና ወደዚህች ምድር መጥቶ የሰዎች ልጆችን ያዳነበት ምስጢር እጅግ ረቂቅ ጥልቅ ነው፡፡ አምላካችን ለኛ ያለውን ፍቅሩን የገለጠው ክብሩን በውርደት ለውጦ ነው፤ጠላቶቹ ስንሆን ነው የወደደን፡፡እንግዲህ በጥልቅ መንፈሳዊ ስሜት በእውነት ካስተዋልን አምላክ ሰው የመሆኑ ምስጢርና ለቤዛነት የመጣበትን ዓላማ በቃልና በድርጊት የፈፀማቸውን ስራዎች ስናስብ ልባችን በቅንነትና በማስተዋል የተመላ ከሆነ ዘወትር ይህንን ቃላት ሊገልጹት የማይችሉትን ለኛ ያለውን ወደር የማይገኝለትን ፍቅሩን ለማድነቅ እንገደዳለን፡፡
 
 “ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ወአብፅሖ እስከለሞት” ፍቅር ኃያል ወልድን ከዙፋኑ
አወረደው እስከ ሞትም አደረሰው ተብሎ እንደተፃፈ፡፡የሰዎች ልጆችን ከባርነት ወደ ነፃነት፣ከመከራ ወደ ደስታ፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ለመግባት ያስቻላቸው የመድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደር የማይገኝለት ታላቅ ፍቅሩ ነው፡፡ስደት እና መንገላታት ውረደት እና በጥፊ መመታት፤መናቅ በብረት መቸንከር እነ በጦር መወጋት ለሰባኪው እና ለሰሚዎች፣ለፀሀፊው እና ለአንባቢዎች ቀላል መስሎ ቢታየንም አምላካችን ስለኛ ብዙ መከራ ተቀብሎ ህይወትን ሰጥቶናል፡፡ከፍ ያለው ፍቅሩ በክብደት መለኪያዎች ተመዝኖ ይህን ያህላል አይባልም፡፡ወርድ እና ቁመቱም ግምቱም አይታወቅም፡፡