Thursday, May 7, 2015

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ያስገነባው መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤት ተመረቀ


001deb002deb
የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ብርሃን ከተማ ያስገነባው ለመንበረ ጵጵስና እና ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚውል ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሚያዝያ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቀ፡፡


በሀገረ ስብከቱ የተገነባውን ሕንፃ ለመመረቅ ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎች ከአዲስ አበባ ወደ በደብረ ብርሃን ሲመጡ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የሃያ ዘጠኝ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዞኑ እና የከተማው የመንግሥት ባለሥልጣናት፤ እንዲሁም የደብረ ብርሃን ከተማ ምእመናን አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡

003deb004deb
ቅዱስነታቸው ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን ሕንፃውን ከመረቁ በኋላ አገልግሎት የሚሰጡትን ክፍሎች በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬምና በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እየተመሩ ጎብኝተዋል፡፡

በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ደባባይ በተከናወነው መርሐ ግብር ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በደብረ ብርሃን ከተማ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እየተሠሩ ያሉ የልማት ሥራዎች የሚያስደስቱ ናቸው፡፡ ከመንበረ ጵጰስናው ግንባታ በተጨማሪ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ደባባይ እየተገነባ የሚገኘው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃም ሀገረ ስብከቱ ለሚያከናውነው መንፈሳዊ አገልግሎት ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ተጨማሪ ሀብት የሚያስገኝ በመሆኑ ሌሎችም አህጉረ ስብከቶች ከዚህ ልማት ሊማሩ ይገባል ብለዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ዘውዱ በየነ ባቀረቡት ሪፖርት በሀገረ ስብከቱ 29 ወረዳ ቤተ ክህነት፤ 2000 አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉ የገለጹ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ360 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ወደ ሀገረ ስብከቱ ከመጡ በኋላ እንደታነጹ አብራርተዋል፡፡

006deb005deb
ለካህናት ሥልጠና በመስጠት፤ የሰበካ ጉባኤ ክፍያን በማሳደግና በማሰባሰብ፤ ስብከተ ወንጌል በማስፋፋት፤ መምህራንን በማፍራትና በመመደብ፤ በአረንጓዴ ልማት፤ በደብረ ብርሃን ሥላሴ ሰባት መምህራንን በመመደብ በአብነት ትምህርት በርካታ ደቀ መዛሙርትን በማፍራት፤ የካህናት ደመወዝን በማሳደግ ሀገረ ስብከቱ አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

ቀድሞ የነበረው የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በንግድ ማእከላት አካባቢ በመሆኑና ምቹ አገልግሎት ለመስጠት ባለማስቻሉ ሌላ ባለ ሁለት ፎቅ መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤትን አጠቃሎ የያዘ ሕንፃ በመገንባት ለዛሬው ምረቃ መብቃቱን ያብራሩት ሥራ አስኪያጁ ባለ አምስት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርታቸው ከተዳሰሱት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ወረብ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ያሬዳዊ መዝሙር፤ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡
010de009deb