Saturday, March 5, 2016

ዘወረደ
የዓቢይ ጾም አንደኛው ሰንበት ዘወረደ ይባላል፡፡ አባታችን ቅዱስ ያሬድ "ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ…ከሰማየ ሰማያት ከልዕልናው ወርዶ ሰው የሆነን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፤ ወይንስ የፍጥረታት ሁሉ ጌታ በቃሉ ሕይወትን የሚሰጥ በቃሉ የሚያድን አምላክ መሆኑን አላወቁ ኑሯል!" ብሎ ጾመ ድጓውን ስለጀመረ ዕለቱ ዘወረደ  ተብሏል፡፡ ዓቢይ ጾም መባሉ ጌታችን  መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለጾመው ነው፡፡ ሁዳዴ ጾም መባሉም ሑዳዴ በሚባለው ጥንታዊ የእርሻ መሬት ስም ታላቅነቱን ለመግለጽ ነው፡፡ ሲወርድ ከየካቲት ፪ ቀን ሲወጣ ከመጋቢት ፮ ቀን ጀምሮ እስከ በዓለ ትንሣኤ ዋዜማ ያለው ፶፭ ቀን ዓቢይ ጾም ይባላል፡፡

በዚህ ቀን ስለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወደ ምድር መውረድ የሰው ልጅ በትሕትና፣ በፈሪሃ እግዚአብሔር ስለመኖር ይዘመራል፡፡ ከሰኞ ጀምሮ ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ሰው ለጾም ልቡን እንዲያዘጋጅ ትምህርት የሚሰጥበት እንዲሁም በጾም ወቅት ሊኖረን ስለሚገባ ሕይወት የምንማርበት ሳምንት ነው፡፡

የዕለቱ የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ርዕስ

ተቀነዩ ለእግዘአብሔር በፍርሃት (ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ)
በቅዳሴ ሰዓት የሚነበቡ የመጽሐፍ ክፍሎች

ንባብ
አንባቢ
1
ዕብ ፲፫:፯-፲፯
ዲያቆን (ገባሬ ሰናይ)
2
ያዕቆብ ፬: ፮
ዲያቆን (ንፍቅ ዲያቆን)
3
የሐዋ ሥራ ፳፭:፲፫
ረዳቱ ቄስ (ንፍቅ ካህን)

የዕለቱ ምስባክ
ተቀነዩ ለእግዚአብሔር በፍርሃት
ወተሐሰዩ ሎቱ በረአድ
አጽንዕዋ ለጥበብ ከመ ኢይትመአዕ እግዚአብሔር

ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ
ለእርሱም በመገዛታችሁ  ደስ ይበላችሁ 
ጌታ እንዳይቆጣ ትእዛዙን ጠብቁ
መዝ ፪፡ ፲፩
ትርጉም
ለእግዚአብሔር በፍርሃት በመንቀጥቀጥ ተገዙ፡፡ በመገዛታችሁም ደስ ይበላችሁ ዋጋ ያለበት ስለሆነ፤ ከፍቅር በመነጨ ፍርሃት ደስ ይበላችሁ፡፡ ለእግዚአብሔርም ተገዙ ጥበበ ወልድን እመኑ ወንጌልን ብሠራላችሁ አልተቀበላችሁም ብሎ እንዳይፈርድባችሁ በልጁ እመኑ፡፡
የዕለቱ ወንጌል፣ ዮሐ ፲፫፡ ፲-፳፭
ቅዳሴ፡ ዘእግዚእነ (ነአኵተከ)

የዕለቱ ትምህርት
ፈሪሃ እግዚአብሔር
1.         ሥጋዊ ፍርሃት ከኃጢአት በኋላ ተከስቷል፤ በጥላቻና መንቀጥቀጥ የሚሆነው የውስጥ ፍርሃት ሰው ሕገ አምላክን ሲተላለፍ ተጀምሯል፡፡ ይህ ዓቢይ ፍርሃት እና ረአድ ወደ ዓለም ከኃጢአት በኋላ ስለመግባቱ (ዘፍ ፫፡፲ ፡፡ ምሳ ፳፰፡ ፩) ላይ እናነባለን፡፡ ክርስቲያን ግን የእግዚአብሔርን ፍቅር ስለሚያውቅ ከእንደዚህ ያለ ፍርሃት በክርስቶስ ነጻ ወጥቷል፡፡ (ሮሜ ፰፡፲፭ ፡፡ ዮሐ ፬፡፲፰)
2.     ፈጣሪን ለማክበርና በፍቅር ላይ የተመሰረተች ፈሪሃ እግዚአብሔር በኃጢአት ምክንያት ከተፈጠረው ፍርሃት የተለየ ነው፡፡ ይህ ፍርሃት ከፍቅር፣ ከአክብሮት የመነጨ መሆኑ ለምስጋና ለቅዳሴ የሚያተጋ በመሆኑ በገነት በነበረው ሰው ሕይወት ውስጥ ነበረ፡፡ ሰው ይህን ቅዱስ ጸጋ በሰይጣን ምክር ሲነጠቅ በድፍረት ኃጢአትን ሠራ፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔር የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ ናት፡፡ ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር እንዳለ ዳዊት፡፡ አክሎም በመዝሙር ፴፫፡፩ ሊያስተምረን ፈቅዶ "ንዑ ደቂቅየ ወስምዑኒ  ፈሪሃ እግዚአብሔር እምሀርክሙ…ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት ላስተምራችሁ " ይላል፡፡

የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ የተባለችበት ምክንያት ሰው እግዚአብሔርን ከፈራ እንደ አብርሃም የታዘዘውን ሁሉ ያደርጋል፡፡ እግዚአብሔርን ፈርቶ የሠራው ሥራም ሞገስ ይሆነዋል፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት ኑ ላስተምራችሁ ያላቸው ልጆቹን ሊያስተምር "ይትዐየን መልአከ እግዚአብሔር ዐውዶሙ ለእለ ይፈርህዎ ወያድኅኖሙ…የእግዚአብሔር መልአክ እግዚአብሔርን በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይከባል፣ ያድናቸውማል" በማለት ፈሪሃ እግዚአብሔር በመላእክተ እግዚአብሔር እንደምታስጠብቀን ተናገረ፡፡ መዝ ፴፫፡ ፯
ፈሪሃ እግዚሀብሔርም ሕይወትን ለሚፈቅድና በጎ ዘመንን ለማየት የሚወድ ጠቃሚ መሆኑን እያስገነዘበ ሲተረጉም እግዚሀብሔርን የምትፈራ ከሆነ በጎ ዘመንንም ለማየት ከፈለግህ አንደበትህን ከክፉ ከልክል ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ ከክፉ ሽሽ፤ መልካምን አድርግ ሰላምን እሻ ተከተላትም አለ፡፡ (መዝ ፴፫) በፈሪሃ እግዚአብሔር የተጠመቀው ዳዊት "የሚፈሩት አንዳችን አያጡም ቅዱሳኑ ሁሉ እግዚአብሔርን ፍሩት" አለ፡፡ በዐስራ አንደኛው መዝሙሩም "እግዚአብሔርን የሚፈራ ትእዛዙንም እጅግ የሚወድ ሰው ምስጉን ነው ዘሩም በምድር ላይ ኃያል ትሆናለች" ብሏል፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያላቸው ሰዎችም ከደፋሮች ይልቅ ክቡራን መሆናቸውን እነርሱንም የሚያከብር እንደሚከብር ሲናገር "ዘያከብሮሙ ለፈራህያነ እግዚአብሔር" እግዚአብሔር የሚፈሩትን የሚያከብር ይከብራል፤ በእግዚአብሔር ድንኳን ያድራል አለ፡፡
ልጁ ሰሎሞንም እግዚአብሔርን ፍራ፤ ትእዛዛቱንም ጠብቅ አለ፡፡(ምሳ ፰) እግዚአብሔርን የሚፈራው የመቶ አለቃ ጸሎቱ ተሰማለት ለአሚነ ክርስቶስም በቃ (የሐዋ ሥራ ፲፡፪)
አንባቢ ሆይ፡
እንግዲያውስ እኛ ወንጌልን እንዳልተቀበሉ በክስቶስም እንዳላመኑ ለፍርድ እንደተጠበቁ ሰዎች ከድንጋጤና ከጭንቀት የሚፈጠረውን ፍርሃት አስወግደን ከዚህ ዓይነቱ ፍርሃት ክርስቶስ ነጻ እንዳወጣን ተገንዝበን የእግዚአብሔርን ፍቅር ቅድስናና ክብር በሚገልፀው ፈሪሃ እግዚአብሔር እንቁም፡፡
ቅዱስ ጳውሎስም "በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ" ይላል (ፊልጵ ፪፲፡፪) ቅዱስ ጴጥሮስም "በእንግድነታችሁ ዘመን በፍርሃትና በፍቅር ኑሩ" ይላል (፩ጴጥ ፩፡፲፯) በዕብ ፲፫፡፯ ላይ ደግሞ "የማይናወጥን መንግስት ስለምንቀበል በማክበርና በፍርሃት እግዚአብሔርን ደስ እያሰኘን የምናመልከበትን ጸጋ እንያዝ አምላካችን በእውነት የሚያጠፋ እሳት ነውና" ይላል፡፡
"እምኅቡዓትየ አንጽሐኒ ወእም ነኪር መሐኮ ለገብርከ" እናዳለ በመለኮታዊ ጥባቆቱ ከድፍረት ኃጢአት እግዚአብሔር እንዲያድነን እንጸልይ እንማጸነው፡፡ (መዝ ፲፰፡፲፫) …ከእኔም ፈቀቅ እንዳይሉ መፈራቴን በልባቸው ውስጥ አኖራለሁ ለእነሱም መልካም ማድረግ ደስ  ይለኛል" ብሎ የነገረውን የተስፋ ቃል እንዲያወርሰን (ኤር ፴፪፡፵) ከፍቅር የተነሳ እንፍራው እናክብረው፡፡ የአጋንንት ዓይነት ፍርሃት ሳይሆን አባታችን ስለሆነ ክብርን ንጉሣችን ስለሆነ ፍርሃትን ይዘን ለእርሱ በፍቅር እንገዛለት፡፡
"ልጅ አባቱን ያከብራል ባሪያም ጌታውን ይፈራል፤ እኔስ አባት ከሆንኩ ክብሬ ወዴት አለ? ጌታስ ከሆንኩ መፈራቴ ወዴት አለ?" እንዳንባል፡፡ (ሚልክያስ ፲፮፡፯)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር…አሜን፡፡
ከመምህር ልዑለቃል አካሉ ሥርዓተ አምልኮ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መጽሐፍ በመጠኑ ተሻሽሎ የቀረበ


Monday, February 15, 2016

ተረፈ ካም

ካም ከሦስቱ የኖህ ልጆች ሁለተኛው ነው፡፡ ሴም ታላቅ ወንድሙ ያፌት ደግሞ ታናሹ፡፡ የጥፋት ውሃ ጎድሎ ምድርም ፈጽማ ከደረቀች በኋላ “አኀዘ ኖህ ይትገበራ ለምድር”  ኖህ ምድርን ይኮተኩታት ይቆፍራት ያርማት ጀመር፡፡ የወይን ሐረግም ተከለ፡፡ ከዚያው ከተከለው ወይን ጠጥቶ ሰከረ፡፡ በድንኳኑ ውስጥም ታራቆተ ፡፡


" ወርእዮ ካም አቡሁ ለከነዓን ዕርቃነ አቡሆሙ ሰሐቀ ወወፅአ ወነገሮሙ ለክልኤሆሙ አኃዊሁ በአፍአ" (የከነዓን አባት) ካምም የአባታቸውን ዕርቃን አይቶ ሳቀ፤ ተሳለቀ፡፡ ወደ ውጭ ወጥቶም ለሁለቱ ወንድሞቹ ነገራቸው፡፡ 

"ወነሥኡ ሴም ወያፌት ልብሰ ወወደዩ ላዕለ ዘባናቲሆሙ ወሖሩ ድኅሪተ ወከደኑ ዕርቃነ አቡሆሙ" ያፌትና ሴም ልብስ ወስደው ሁለቱም በትከሻቸው ላይ አደረጉ፡፡ የኋሊት ሄደው የአባታቸውን ዕርቃን ሸፈኑ፡፡ በዓይኖቻቸው የአባታቸውን እራቁትነት ለማየት እንኳን አልደፈሩም፡፡

"ወገፆሙ ድኅሬሆሙ አግብኡ ወኢርእዩ ዕርቃነ አቡሆሙ" ይላል፡፡ ፊታቸውን ወደ ኋላ አዙረው ወጡ፡፡ የአባታቸውን እርቃን አላዩም፡፡

ከዚህ በኋላ የወይን ስካር ፈጽሞ አእምሮ አይነሳምና ኖህ ከስካሩ ነቃ  ታናሹ ልጁ ካም እንደዘበተበት፤ ያፌትና ሴም ልባሳቸውን እንዳለበሱት ባወቀ ጊዜ በታናሹ ልጁ ካም አዘነበት፤

Monday, January 25, 2016

ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን

                                                 
    ቤተ ክርስቲያን ማለት ሕንፃው፣ የክርስቲያኖች አንድነት /ጉባኤ/ እና የምዕመኑ ሰውነት በመሆኑ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የምንለውም በእነዚህ በሦስቱ ላይ የተሠራውን ሥርዓት ነው። አንዳንዶቻችን ቤተ ክርስቲያንን ከራሳችን አርቀን ሌላ አካል አድርገን ስለምንመለከት ሥርዓቱ እኛን የሚመለከት አይመስለንም። ሥርዓቱ ግን የተሠራው ለሦስቱም የቤተ ክርስቲያን ትርጓሜዎች መሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው።
  ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ምንጩ ወይንም መሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ፣ የቅዱሳን አባቶቻችን ጉባኤያት ውሳኔ /ሲኖዶስ/ እና አባቶቻችን ሊቃውንት በተለያዩ ጊዜ ያደረጓቸው ጉባኤያት ውሳኔዎች ናቸው።

Monday, January 18, 2016




                         እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ!
 

                                    ገሃድ/ ጾመ ድራረ ጥምቀት

    
ገሃድ የቃሉ ትርጉም መገለጥ መታየት ነው፡፡ በጥምቀት መገለጥ መባሉ ሰው የሆነው አምላክ በዓለም ሲኖር እስከ 30 ዓመት እድሜው ድረስ ሰዎችን ለማዳን የመጣ መሲህ ሰው የሆነበት፣ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ እሱ መሆኑን ሳያውቁ ከኖሩ በኃላ 30 ዓመት እድሜው በባሕረ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ እጅ ሲጠመቅ አብ በደመና ሆኖ ‹‹የምወደው ልጄ ይህ ነው›› በማለቱ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲያርፍ በመታየቱ ነቢያት ይወርዳል ይወለዳል ይሰቀላል ይሞታል ይነሳል ብለው የተናገሩለት መሲሕ እርሱ መሆኑ ተገልጦአልና እንዲሁም ሦስቱ አካላት በአንድ ጊዜ ታይተዋልና ምስጢረ ሥላሴ የተገለጠለት በመሆኑ ገሃድ ይባላል፡፡(ማቴ 313-17)
ይህን በማሰብ የምንጾመው ጾምየገሃድ ጾምይባላል፡፡ ቀኑም ጥር 10 ቀን 11 አጥቢያ ነው፡፡ስለዚህ ጥር 10 ቀን ሰባቱ አጽዋማ አንዱ የሆነው የገሀድ ጾም ነው ማለት ነው!

ዚቅ ዘጥምቀት ወቃና ዘገሊላ

ውድ የጦማራችን ተከታታዮች እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ እያልን ከሊቃውንቱ ጋር በመቆም ከበዓሉ በረከት ተካፈይ ትሆኑ ዘንድ ከከተራ በዓል (ከዋዜማው) ጀምሮ እስከ ቃና ዘገሊላ ድረስ ያለውን የማኅሌት ሥርዓት ከዚህ እንደሚከተለው  ከመጽሐፈ ዚቅ በማውጣት በጽሑፍ አቅርበንላችኋል።

ዋዜማ

ሃሌ ሉያ ኃዳፌ ነፍስ ለጻድቃን ወተስፋ ቅቡጻን፤
ክርስቶስ አስተርአየ ውስተ ዓለም፤
እምድንግል ተወልደ ክሡተ ኮነ፤
እንዘ ይትዔዘዝ ለአዝማዲሁ፤
ከዊኖ ሰብአ በዮርዳኖስ ተጠምቀ ፡፡

በሐምስተ

በዮርዳኖስ ተጠምቀ ፈጺሞ ሕገ፤
ወአስተርአየ ገሃደ በዮርዳኖስ ተጠምቀ፡፡

እግዚአብሔር ነግሠ

አስተርእዮ ኮነ ዘክርስቶስ ስነ መለኮት፤
ከመ ርግብ ውስተ ምጥማቃት እንዘ ይብል ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ፡፡

ይትባረክ
 

ርእዩከ ማያት እግዚኦ