Monday, July 4, 2016

                                                 ክረምት


          በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ በዕለተ ረቡዕ የተፈጠሩት ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ቀን ለመቁጠር፣ዘመንን፣ ወራትን፣ በዓላትንና አጽዋማትን ለማወቅ ወሳኝ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ ዘፍ.14-19፣ ዘዳ.12፡1፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አቆጣጠር አንድ ዓመት በፀሐይ አቆጣጠር 365 1/4 ቀናት፡፡ በጨረቃ አቆጣጠር 354 ቀናት፡፡ በከዋክብት አቆጣጠር ጸደይ፣በጋ፣መጸውና ክረምት የተባሉ አራት ወቅቶች አሉ፡፡

ወቅት እንዲፈራረቅ በዘመን ላይ የተሾሙ ዓመቱን በአራት ክፍለ ዘመን የሚገዙት አራት ከዋክብት ሲሆኑ በእያንዳንዱ ወር ላይ የሰለጠኑ ከአራቱ ከዋክብት ሥር እንደ ወታደር የሚያገለግሉ ሦስት ሦስት ወታደሮች በድምሩ 12 ከዋክብት አሉ፡፡ እነዚህ ከዋክብት ወቅቶቹ ሥርዐታቸውን ጠብቀው እንዲሸጋገሩ የሚያደርጉና የእግዚአብሔር ጸጋ ለፍጥረቱ እንዲደርስ የሚያደርጉ ናቸው፡፡

ዓመቱን ለአራት ወቅቶች የሚከፈሉትና የሚመግቡት ከዋክብት የሚከተሉት ናቸው፡-
ምልክኤል፡-
በጸደይ የሰለጠነው ኮከብ ምልክኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት/ወታደሮች/ ሚዛን በመስከረም ወጥቶ 30 ዕለት ከ 10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ሚዛን ነው፡፡ አቅራብ በጥቅምት ወጥቶ 29 ዕለት ከ40 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ጊንጥ ነው ፡፡ ቀውስ በኅዳር ወጥቶ 29 ዕለት ከ28 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ቀስት ነው፡፡ (ኬኪሮስ ማለት ረጅም መስመር ማለት ሲሆን የቀንና የሌሊት ሰዓቶች ክፍል ነው፡፡ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ተዘርግቶ 60 ክፍሎች አሉት፡፡ ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት ሁል ጊዜ እየሄዱበት በየቀኑ አንድ ጊዜ ያልፍበታል፡፡ 5 ኬክሮስ 1 ሰዓት ነው፡፡)

Friday, July 1, 2016

                   አባ ሙሴ ጸሊም 




ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙ ቅዱሳንን ከተለያየ ዓለማዊ ሥራ ጠርቶ ቃሉን ለመስበክ፣ ስሙን ለመቀደስና ክብሩን ለመውረስ ያበቃቸው ቅዱሳን ብዙዎች ናቸው፡፡
በዛሬው ዝግጅታችን በኃጢአት ሕይወት ከኖሩ በኋላ በንስሓ ከተመለሱ ቅዱሳን መካከል አንዱ የኾኑትን በዓለ ዕረፍታቸው ሰኔ ፳፬ ቀን የሚዘከረዉን የአባ ሙሴ ጸሊምን ታሪክ በአጭሩ እናቀርብላችኋለን፡፡

Thursday, June 9, 2016

     ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 
            ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
                                                                                ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

           የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፭ ቍጥር ፻፷፬ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የዘንድሮዉን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ የጉባኤው መክፈቻ ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረ ለዐሥራ ስድስት ቀናት ያህል ባደረገው ጉባኤ ጠቀሜታ ባላቸው የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

Tuesday, April 12, 2016

ሚያዝያ 6 ቀን የቅዱስ አዳም እና የቅድስት ሔዋን ዓመታዊ የዕረፍት መታሰቢያ በዓላቸው ነው!!! በረከታቸው በኛ ላይ ይደርብንና እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ኑሮ የሚያስፈልጉ ነገሮችን ከፈጠረለት በኋላ በስድስተኛው ቀን ዐርብ የመጀመርያውን ሰው አዳምን ፈጠረ። እግዚአብሔር ሲፈጥረውም በእራሱ መልክ እና ምሳሌ ፈጠረው፤ በምድር ላይ ለሚኖሩ ፍጥረታት ሁሉ ገዢ አደረገው። እግዚአብሔርም አዳም ብቻውን በመሆኑ ከጎኑ አጥንትን ወስዶ ሔዋንን ፈጠራት። በተፈጠሩበት ምድር አዳም አርባ ቀን ፣ ሔዋን ደግሞ ሰማንያ ቀን ከቆዩ በኋላ ወደ ኤዶም ገነት አስገባቸው። ይህን መሠረት አድርጋ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ወንዶች በተወለዱ በአርባ ቀናቸው ፣ ሴቶች በተወለዱ በሰማንያ ቀናቸው ተጠምቀው የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ታደርጋለች። እግዚአብሔርም በገነት መካከል ያሉትን ፍሬዎች እንዲበሉ ፈቀደላቸው። ነገር ግን ዕፀ በለስ ተብላ የምትጠራውን ፍሬ እንዳይበሉ አዘዛቸው። ከዚህች ፍሬ ብትበሉ የሞት ሞትን ትሞታላችሁ ብሎ አስጠነቀቃቸው። አዳምና ሔዋን የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ አክብረው ለ7 ዓመት ያህል ገነት ኖሩ። ሰይጣን ዲያብሎስ በእባብ በኩል የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ እንዲያፈርሱ ፈተና አመጣባቸው። ዲያብሎስ በእባብ አድሮ ወደ ሔዋን ቀርቦ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት። እሷም ዕፀ በለስን ብትበሉ ትሞታላችሁ እንደተባሉ ነገረችው። እባብም ለሔዋን ሞትን አትሞቱም ከእርስዋ በበላችሁ ጊዜ እንደ እግዚአብሔር ትሆናላችሁ ብሎ በሀሰት አታለላት። ሔዋንም የእባብን ሽንገላ ሰምታ እውነት እንደ እግዚአብሔር የሚሆኑ መስሏት ለመብላት ወሰነች። ከፍሬውም ወሰደችና ከባልዋ ከአዳም ጋር አብረው በሉ። በበሉም ጊዜ ጸጋቸው ተገፈፈ፣ የክብር ልብሳቸውን አጡ፣ እነርሱም ዕራቁታቸውን እንደ ሆኑ አወቁ፤የበለስን ቅጠል ሰፍተው ለበሱ። የእግዚአብሔርን ሕግና ትእዛዝ ስናፈርስ ጸጋችን ይገፈፋል፤ እግዚአብሔርም ያዝንብናል። አዳምና ሔዋንም የእግዚአብሔርን ድምፅ ሲሰሙ ፈርተው በገነት ዛፎች መካከል ተሸሸጉ። እግዚአብሔርም አዳምን ጠርቶ፦ ወዴት ነህ? አለው። እርሱም በገነት ድምፅህን ሰማሁ ዕራቁቴንም ስለ ሆንሁ ፈራሁ፥ ተደበቅሁም አለው። እግዚአብሔርም ዕራቁትህን እንደ ሆንህ ማን ነገረህ? ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝሁህ ዛፍ በላህን? ሲለው አዳምም ከእኔ ጋር እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት እርስዋ ከዛፉ ሰጠችኝና በላሁ አለው። እግዚአብሔርም ሁላቸውንም በጥፋታቸው ምክንያት ረገማቸው። እግዚአብሔርም እባቡን ይህን ስላደረግህ ከእንስሳት ፣ ከምድር አራዊትም ሁሉ ተለይተህ አንተ የተረገምህ ትሆናለህ በሆድህም ትሄዳለህ፥ አፈርንም በሕይወትህ ዘመን ሁሉ ትበላለህ ብሎ ረገመው። ሔዋንንም በፀነስሽ ጊዜ ጭንቅሽን እጅግ አበዛለሁ በጭንቅ ትወልጃለሽ ፈቃድሽም ወደ ባልሽ ይሆናል፥ እርሱም ገዥሽ ይሆናል ብሎ ረገማት። አዳምንም እንዳትበላ ካዘዝሁህ ዛፍ በልተሃልና ወደ መጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ አፈር ነህና፥ ወደ አፈርም ትመለሳለህና ብሎ ረገመው። እግዚአብሔርም በበደላቸው ምክንያት ከረገማቸው በኋላ ከ ገነት አስወጣቸው፥ አዳምም የተገኘባትን መሬት አርሶ መብላት ጀመረ። አዳምና ሔዋን ከገነት ከወጡ በኋላ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ፣ ገነትን ያህል ቦታ በማጣታቸው በሰሩት ኃጢአት ተጸጽተው እግዚአብሔር እንዲምራቸው ሱባኤ (ጸሎት) ያዙ። እግዚአብሔር ጸሎታቸውን እና ልመናቸውን ተመልክቶ እንደሚምራቸው ቃል ኪዳን ገባላቸው። ቃል ኪዳኑም “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ከ5500 ዘመን በኋላ አድንሃለሁ” የሚለው ነበር። ቅዱስ አዳም ሚያዝያ 6 ቀን በ930 ዓመቱ ዕድሜ ጠግቦ አረፈና በቀራንዮ ተቀበረ። እግዚአብሔርም እንደተናገረ አልቀረም ከእናታችን ድንግል ማርያም ተወልዶ አዳምን ከእነ ልጅ ልጆቹ አዳነን። በአጠቃላይ ከአዳምና ሔዋን ታሪክ የምንማረው አታድርጉ የተባልነውን ነገር ማድረግ እንደለለብን ፤እሱን አልፈን ግን ብናደርግ እስከ ሞት ድረስ መከራ ሊያመጣብን እንደሚችል መረዳት አለብን። እግዚአብሔር ደግሞ የይቅርታና የምሕረት አምላክ እንደሆነ እንረዳለን። ስለዚህ ለእግዚአብሔር ሕግና ትእዛዝ መታዘዝ ይኖርብናል።

Thursday, March 10, 2016

አርጋኖን

የመዝሙር መሳሪያዎች በተነሳ ቁጥር ይሄ አርጋኖን የተሰኘ የዜማ እቃ በቤተክርስቲያን አባቶችና አንዳንድ ሰዎች ዘንድ ልዩነት እየፈጠረ እስከአሁን ቆይቷል፡፡ በቅርቡ የአሜሪካው "ሲኖዶስ" ዋና ጸሐፊ የሆኑት አቡነ መልከጼዴቅ አርጋኖን/ኦርጋን ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የምስጋና ዕቃ እንዲሆን  አውጀዋል፡፡ እንዲህ ነው አንዲያ ነው ከማለት በፊት የአርጋኖንን ጥነተ ነገሩን ጥንተ መሠረቱን መመርመር ተገቢ ነው፡፡

ኦርጋኖንአርጋኖን የግሪክ ቃል ሲሆን ጥሬ ትርጉሙ መሣርያ ማለት ነው፡፡ ጥንታዊው የግሪክ ፈላስፋ አሪስቶትል (አሪስጣጣሊስ) ኦርጋኖን የሚለውን ቃል የስነ አመክንዮ መሳሪያ ወይም የሐሳብ መግለጫ መንገድ ዘዴ በማለት ቃሉን ተጠቅሞታል፡፡ነገር ግን በ3ኛው መ/ክፍለ ዘመን ቅ.ል.ክ ክቲሲቢዮስ ዘእስክንድርያ የተባለ ግሪካዊ ተመራማሪና መሐንዲስ ሃይድሮሊስ (የውሃ ኦርጋን) የተሰኘ የዜማ መሣሪያ ከፈለሰፈ በኋላ ኦርጋኖን የሚለው ቃል የዜማ ዕቃ/መሣሪያ የሚለውን ትርጉም ጨምሮ ወርሷል፡፡ ይህ የሙዚቃ መሣርያ በጥንት ዘመን የአደባባይ መዝናኛ በዓላት ማድመቂያ በመሆን በሰፊው  አገልግሎት ይሰጥ እንደነበር በታሪክ መጻሕፍት ተመዝግቧል፡፡ በተደረጉ የአርኪዮሎጂካል ቆፋሮዎችም ይህ ሁለት ሺህ ሦስት መቶ አመት ገደማ ያስቆጠረ ጥንታዊ መሳሪያ ከተቀበረበት ወጥቶ በአውሮፓ ሙዚየሞች ለእይታ በቅቷል፡፡ ነገር ግን ከ 5ኛው ክፍለ ዘመን ድ.ል.ክ በኋላ ተቀባይነቱ ቀንሶ በሌሎች እርሱን መሰል የተሻሻሉ መሳሪያዎች (ፓይፕ ኦርጋን፣ ሪድ ኦርጋን፣ ቸርች ኦርጋን) ተተክቷል፡፡ ይህ ሃይድሮሊስ ወይም ኦርጋኖን የተባለ የዜማ መሣሪያ አሁን ኦርጋን ለተሰኙት ባለቁልፍ ሙዚቃ መሣሪያዎች ቅድመ አያታቸው ነው፡፡ ስለዚህ ኦርጋኖን/አርጋኖን በዘመናችን ኦርጋን የሚለው ቃል ይተካዋል፡፡ አርጋኖንን በገና ብለው የተረጎሙ አሉ፡፡ ይህ ማለት ግን አርጋኖን በገና ነው አያሰኝም፡፡በገና የክር መሰሪያ ሲሆን አርጋኖን ደግሞ ከቁልፍ መሣሪያዎች ጎራ የሚመደብ ነው፡፡ አርጋኖን ኦርጋን አደለም ብሎ መሟገትም አያዋጣም፡፡

እንግዲህ ስለ አርጋኖን አመጣጥ ይህን ካልን፡፡ ሊቃውንት ቤተክርስቲያን ስለ አርጋኖን ምን እንዳሉ እንመልከት፡፡ አርጋኖን የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድ በዜማ ድርሰቶቹ ጠቅሶታል፡፡
ሰባኬ ወንጌል ዮሐንስ አርጋኖነ ትንቢት ዘይደምጽ ለቤተ ክርስቲያን…ወንጌልን የምትሰብክ ዮሐንስ ለቤተክርስቲያን ሰናይ ድምጽን የምታሰማ የትንቢት አርጋኖን ነህ በማለት ቅዱስ ያሬድ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድን በድጓው አወድሷል፡፡ በተጨማሪም በማክሰኞ አርያሙ  ከመ ዝብጠተ መሰንቆ አርጋኖን ስብሐቶሙ ለእሙንቱ ካህናት…የካህናቱ ምስጋና መሰንቆ አርጋኖን ሲመታ እንደሚያወጣው ሰናይ ድምጽ ጣፋጭ ነው ባሏል፡፡

ቅዱስ ያሬድ የካህናትን ጥዑም ድምጽ፣ የሐዋርያትን ስብከት ከአርጋኖን ጋር መስሎ  ይህን ሲል በሁለት መንገድ ልንተነትነው እነችላለን፡፡  አንደኛው  አርጋኖን የሰኘውን የዜማ መሣሪያ ቅዱስ ያሬድ በነበረበት ወቅት አገልግሎት ላይ ስለነበር የመሣሪያውን መልክና ቁመና እንዲሁም ድምጹን ያውቀዋል፤ ሁለተኛው  ደግሞ ቅዱስ ያሬድ ከመጻሕፍት አግኝቶ ለድርሰቱ ውበት ተጠቅሞታል፡፡ ያም ሆነ ይህ አርጋኖን የተባለውን የዜማ መሣርያ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ከመሰንቆ፤ ከእንዚራ ጋር አስተባብሮ ቅዱሳንን ለማመስገን መስሎ አቅርቦታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በነበረበት ዘመን አርጋኖን አግልግሎት ላይ ነበር ለማለት ይቻላል፡፡ እንዲያውም ቅዱስ ያሬድ ለመጀመሪያ ጊዜ ዜማን ሲደርስ ወደ አርያም ተነጥቆ ካያቸውና ከሰማቸው  የዜማ ዕቃዎች አንዱ ኦርጋኖን/ኦርጋን እንደነበር ገድለ ያሬድ ይተርካል፡፡

ወሰምዐ በህየ ቃለ እንዚራ ወቃለ አርጋኖን ወቃለ መሰናቅው እንዘ ይሴብሕዎ ወይዌድስዎ ወየአኵትዎ ለፈጣሬ ሰማያት ወምድር በስብሐት ወበማኅሌት…በዚያም የእንዚራን፣ የአርጋኖንን፣ የመሰንቆን እንዲሁም ሰማይና ምድርን የፈጠረ እግዚአብሔርን በስብሐትና በማኅሌት ሲያመሰግኑት ሰማ፡፡

አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም የቅዱስ ያሬድን የምስጋና ፈለግ ተከትሎ እመቤታችንን በአርጋኖን በመመሰል ብዙ የውዳሴ ድርሰቶችን ለቤተክርስቲያን አበርክቷል፡፡

እንግዲህ ሊቃውንቱ አርጋኖንን እንደ ምሳሌ ከመጠቀም ያለፈ ነገር አልተናገሩም፡፡ የኢትዮጽያ ቤተክርስቲያን አባቶችም ይህ አርጋኖን የተሰኘ የዜማ እቃን ተጠቅመው ሲያመሰግኑ በታሪክ ተመዝግቦ አላገኘንም፡፡ ሆኖም በኦርጋን የሚደርስ ምስጋና የረከሰ እግዚአብሔር የማይቀበለው፤ በዋሽንትና ክራር የሚደረግ ግን የተቀደሰና እግዚአብሔር የሚቀበለው እንደሆነ አድርጎ ማሰብ ግን የተሳሳተ ነው፡፡ መቃወማችን እግዚአብሔር በአርጋኖን/ኦርጋን አይመሰገንም ከሆነ ተሳስተናል፡፡ ምክንያቱም የዜማ ዕቃዎች ሁሉ ሰው ሰራሽ ናቸው፡፡ ከሰማይ የወረደ በገና፤ ከሰማይ የወረደ ከበሮ፤ ከሰማይ የወረደ መሰንቆ የለንም፡፡ ኦርጋንን የሰራው ሰው ነው  በገናውም የሰው ፈጠራ ነው ያውም የመጀመሪያ አላማው ለዘፈን ነበር ዘፍ. 4፡ 21 ፡፡ ዋሽንቱም ብትሉ ጣዖት ማጀቢያ እንደነበር በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፏል ዳን 3፡ 5-7፡፡ ሰው ባለው ባገኘው እንደየባሕሉ ማመስገን ይችላል፡፡ለሰይጣን ንብረት የለውም፡፡ ቁም ነገሩ አጠቃቀማችን ላይ ነው፡፡ ግዴታ በመሰንቆና ዋሽንት ካልሆነ አይባልም፡፡ እግዚአብሔር በከበሮና ጸናጽል በክራርና ዋሽንት ብቻ ካላመሰገናችሁኝ አልቀበልም አላለም፡፡  

ኧረ ለመሆኑ ክራርና ቤስ ክራር እያቀላቀሉ በያሬዳዊ መዝሙር ስም ጆሯችንን ያደነቆሩት ዘማሪዎቻችንን አሜን ብለን ተቀብለን ይኸው በየታክሲው በየመዝሙር ቤቱና በየመሸታ ቤቱ ስናስጮቸው አይደል የምንውለው? የሲኖዶሱ ቀኖናስ ከተሻረ አልሰነበተም ወይ? በየትኛው የሲኖዶስ ጉባዔ ወይም በየትኛው ሐዋርያዊ ቀኖና ነው ክራርና ቤዝ ክራር የመዝሙር መገልገያ ዕቃ ሁነው የተመዘገቡት? አቡነ መልከጼዴቅ በዚህ ነገር ልክ ብለዋል፡፡ ክራሩን ተቀብለን የኦርጋን ነገር ሲነሳ የሚያስነጥሰን ከሆነ ችግር ነው፡፡

ነገር ግን ይህን ሲባል ኦርጋን ቤተክርስያናችን ይግባ ለማለት አይደለም፡፡ ይህን መወሰን የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶሱ ብቻ ነው፡፡ ዲያቆን እገሌ፣ ቄስ እገሌ መምህር እገሌ ስለተናገረ የሚሆን ነገር የለም፡፡ ስልጣኑ የቅዱስ ሲኖዶሱ እና የቅዱስ ሲኖዶሱ ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም በኦርጋን እንድናመሰግን አልፈቀደም፡፡ በተጨማሪም ቤተክርስቲያን ኦርጋንና ሌሎች ዘመነኛ የዜማ ዕቃዎች አያስፈልጓትም፡፡ ያሉት የዜማ ዕቃዎች በቂ ናችው፡፡  ስለዚህ ስርአተ ቤተ ክርስቲያንን ከማስጠበቅ አንጻርና ወደፊት ኦርጋንን ተከትሎ ከሚመጣ ስርአት አልበኝነትና ጋጠወጥነትን እስቀድሞ ከመከላከል ረገድ ኦርጋንና ሌሎች ዘመናዊ የዜማ መሣሪያዎችን ከቤተክርስቲያን ማራቁ ተገቢ ነው፡፡

ሐዋርያት በየትኛውም የዜማ መሳሪያ ተጠቅመው ሲያመሰግኑ አልተመዘገበም፡፡ በዘመነ አበው የነበሩ እነ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ አውሳቢዮስን የመሰሉ  ታላላቅ የቤተክርስቲያን አባቶችም የዜማ መሳሪያን ተጠቅመን የአምልኮ ሥርዓት እንድንፈፅም አላዘዘኑም አላስተማሩንምም፡፡ እንዲያውም በተቃራኒው የሐዲስ ኪዳን አማኝ የሆንን እኛ ክርስቲያኖች ከዜማ መሳሪዎች ርቀን በልባችን እንዚራ በአንደበታችን መሰንቆ ብቻ ማመስገን እንደሚገባን ሰብከዋል፡፡


ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡